tg-me.com/orthodox1/13289
Last Update:
"ብእሲት ዘኃደገት ቀሱታ ⇨ መቅጃዋን የተወችው ሴት"
°°°°°°°°°°°°°°°°°°°°°°•◇•°°°°°°°°°°°°°°°°°°°°°°°
ከሰማርያ መንደር ከወጡ ደገኛ የቅዱስ መጽሐፍ ባለ ታሪኮች ደጉ ሳምራዊ እና ደጓ ሳምራዊት ጎልተው ይጠቀሳሉ። በመጽሐፈ ስንክሳራችንም መጋቢት ፭ ቀን የስሟ ትርጓሜ ሰላምና ሥምረት የሆነ ቅድስት አውዶክስያ የምትባል አንዲት ሳምራዊት ሴት በታላቅ ተጋድሎ ማረፏን ይነግረናል።
የደጉ ሳምራዊ ታሪክ ለትምህርት ምሳሌ ነው [የሉቃስ ወንጌል 10:33] ፤ የእርሷ ግን በአምላካችን ዘመነ ሥጋዌ የተፈጸመ አስተማሪ ኩነት አዝሏል። መኖርያዋ ሲካር ነው ታላቋ «ሳምራዊት» ሴት [የዮሐንስ ወንጌል 4:7]
ይህች ሴት መድኃኔዓለም የሚለውን ስም በወንጌል ቀድሞ በሰው አፍ እንዲጠራ በስብከቷ ምክንያት የሆነች የከበረች ምስክር ናት።
ሰማዕነ ወጠየቅነ ከመ ዝንቱ ውእቱ ክርስቶስ በአማን #መድኅነ_ዓለም
↳ ይህ በእውነት የዓለሙ መድኅን ክርስቶስ እንደሆነ ሰምተናል ተረድተናል
ወንጌል ስለመጨረሻው ተልእኮዋ ሲነግረን እንዲህ ይተርከዋል፦
☞ "ወኃደገት ቀሱታ ይእቲ ብእሲት ወአተወት ሀገረ ወነገረት ለሰብአ ቤታ ። ወትቤ ንዑ ትርአዩ ብእሲ ዘነገረኒ ኵሎ ዘገበርኩ እንዳዒ ለእመኑ ውእቱ ክርስቶስ "
↳ ሴቲቱም ማድጋዋን ትታ ወደ ሀገር ገብታ ለቤተሰቦቿ ነገረች ። የሠራሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ታዩ ዘንድ ኑ፡ ክርስቶስም እንደሆነ እንጃ አለች ።
መምህረ ዓለም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሐዋርያዊ ሥራዋን በላቀ መንገድ ሲነግረን "ሌሎቹ ሐዋርያት መረባቸውን ጥለው ሲከተሉት እርሷም በሐዋርያነቷ መቅጃዋን ጥላ ተከተለችው ከእነርሱ እነ ፊልጶስ እነ እንድርያስ ሌላውንም እንዲከተለው በአንድ በሁለቱ ፊት ሲመሰክሩ እርሷ ግን መንደሩ ሁሉ እንዲከተለው ሰበከች" አለን ፤ አቤት መታደሏ!
ሳምራዊቷ ሴት ማናት?
°°°°°°°°°°°°°°°°°°°°
ከ፹፩ዱ ቅዱስ መጽሐፋችን በተጨማሪ በሌሎች የትውፊት መጻሕፍት አዋልድም ጭምር በተለያዩ መጠሪያዎች ተጠርታ ከተጨማሪ ታሪኮች ጋር እናገኛታለን።
ቀደምት የግሪክ ክታቦች አምስት እኅቶችና ሁለት ልጆች የነበሯት በሰማዕትነት ክብር ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ ጴጥሮስን ተከትላ የጽድቅ ምስክር ሆና ያረፈች እንደሆነች አስረድተው ስሟ የከበረ ታላቋ ሰማዒት (ምስክር) ሳምራዊቷ ቅድስት #ፎጢን (holy and glorious Great-martyr #Photine of Samaria) እያሉ ገልጠዋታል።
የ’ኛውም ተአምረ ኢየሱስ ደግሞ ስሟን በመጥቀስ የታሪኳን ፍጻሜ እንዲህ አስቀምጦልናል ፦
☞ "ወሶበ ሰምአት ብእሲት ሳምራዊት ዘስማ #ብርፍሴንያ ነገሮ ለእግዚእ ኢየሱስ ሖረት ወዜነወት ለሰብእ እንዘ ትብል ንዑ ኀቤየ አርእየክሙ ብእሴ ዘየአምር ኅቡአተ እስመ ውእቱ ዜነወኒ ግብርየ ዘአኀብኦ እም ሰብእ"
↳ ይህችም ብርፍሴንያ የምትባል ሳምራዊት ሴት የጌታ ኢየሱስን ነገር በሰማች ጊዜ ወደሀገር ገብታ ለሰዎቹ ሁሉ በሆዴ ውስጥ ያለውን ምሥጢር ሁሉ የሚናገር ሰው አሳያችሁ ዘንድ ኑ እኔ ከሰው ደብቄ የያዝኩትን ምሥጢር ነግሮኛልና አለቻቸው ።
ሳምራዊቷ ሴት ቅድስት ብርፍሴንያ መቅጃዋን ጥላ ወደ መንደር ተመልሳ በሀገሩ ያሉትን ሁሉ ወደ ድኅነት ወደ ሕይወት ውኃ ጠራች የበረከት ቃል ከአንደበቷ እየተቀዳ አፏ የሕይወት ውኃ ምንጭ ሆነ። "ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ" ትላለች። ጠቢቡ “የጻድቅ አፍ የሕይወት ምንጭ ናት፤ የኀጥኣንን አፍ ግን ግፍ ይከድነዋል።” 【ምሳሌ 10፥11】
ለሲካር መንደር ሕዝብ ቅድስት ብርፍሴንያ ለሕይወት ውኃ ክርስቶስ "መቅጃቸው" ናት። እነርሱ ግን የሴት ደቀ መዝሙር ለመባል አፍረው በእርሷ ስብከት ተከትለው ቢያምኑበትም የእርሷን ድርሻ ግን እንዲህ እያሉ ካዱ ፦
☞ "ወይቤልዋ ለይእቲ ብእሲት አኮ እንከ በነገረ ዚአኪ ዘአመነ ቦቱ አላ ለሊነ ሰማዕነ ወጠየቅነ ከመ ዝንቱ ውእቱ ክርስቶስ በአማን መድኅነ ዓለም ።"
↳ ሴትዮዋንም አሁን በእርሱ ያመን ፡ አንቺ በተናገርሽው አይደለም እኛ ራሳችን ይህ በእውነት የዓለሙ መድኅን ክርስቶስ እንደሆነ ሰምተንና ተረድተን ነው እንጂ አሏት።
የሳምራዊቷን ሴት የቅድስት ብርፍሴንያ [Great-martyr St. Photine]
✧ በረከቷ በሁላችን ላይ ይደር! ✧
BY ኦርቶዶክስ ተዋህዶ - 🇴🇷🇹🇭🇴🇩🇴🇽 🇹🇪🇼🇦🇭🇩🇴
Warning: Undefined variable $i in /var/www/tg-me/post.php on line 283
Share with your friend now:
tg-me.com/orthodox1/13289